ባለስልጣኑ ከደቡብ ኮሪያ ጉምሩክ አገልግሎት ጋር የትብብር ስምምነት ተፈራረመ፤
ባለስልጣኑ ከደቡብ ኮሪያ ጉምሩክ አገልግሎት ጋር የትብብር ስምምነት ተፈራረመ፤
ኢትዮጵያ ከግብርና መር ወደ ኢንዱስትሪ መር ለምታደርገው ኢኮኖሚያዊ ሽግግር የጉምሩክ አሰራር ስነ-ስርዓትን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማገዝ የበለጠ ፈጣንና ቀልጣፋ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡
በዚህም መሰረት የደቡብ ኮርያ ጉምሩክ አገልግሎት እና የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን በጉምሩክ አሰራር ስነ ስርዓት ላይ በጋራ ለመስራት የስምምነት ፊርማቸውን አኑረዋል፡፡
መጋቢት 17/2007ዓ.ም በባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተደረገው ስምምነት ኮሪያና ኢትዮጵያ ትስስራቸው በጉምሩክ አገልግሎት ብቻ ሣይሆን ታሪካዊ የሆነ ግንኙነት እንዳላቸውም የባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ በከር ሻሌ ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከኮሪያ ጉምሩክ አገልግሎት ባለሙያዎች በርካታ ልምዶችንና ሙያዊ ድጋፎችን ልታገኝ እንደምትችል ደግሞ የገለጹት የባለስልጣኑ የጉምሩክ ልማትና ድጋፍ ሥራዎች ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ካይዳኪ ገዛኸኝ ናቸው፡፡
በቀጣይም የደቡብ ኮሪያ ጉምሩክ አገልግሎት እና ባለስልጣኑ የበለጠ ግንኙነታቸዉን በማጠናከር በትብብር እንደሚሰሩ አስታውቀዋል፡፡
የደቡብ ኮሪያ ጉምሩክ አገልግሎት ጄኔራል ኮሚሽነር ሚስተር ሊምናክሆይ በበኩላቸው ኢትዮጵያ ውስጥ በጉምሩክ ላይ ለመስራት በመስማማታቸው እንደተደሰቱ እና ስምምነቱ በሁለቱ አገራት መካከል ያለው የቆየ ግንኙነት እደሚያጠናክር ገልጸዋል፡፡
በባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር የተመራው የልዑካል ቡድን በቅርቡ በኮሪያ የጉምሩክ አገልግሎት ተገኝቶ ጉብኝት ማካሄዱና የመግባቢያ የስምምነት ሰነድ መፈራረሙ ይታወሳል፡፡
በኤፍሬም ብላቱ